.....አዲስ ዓመት የለም
.....አዲስ ዓመት የለም፡፡ ተፈጥሮ በፈጣሪዋ የተደነገገላትን ህግጋት አክብራ ጨረቃ በመሬት መሬት ደግሞ በፀሀይ ዙሪያ የሚያደርጉትን የማያባራ ኡደት ሲፈጽሙ እኛ በበኩላችን መዓልቱን በፀሀይ ሌቱን በጨረቃ አስልተን ለቀናቱ፣ ለወራቱና ለዓመታቱ ስያሜና ቁጥር እየሰጠን የዕለትና የዓመት ተግባራችንን አቅደን ወይም በዘፈቀደ እየፈጸምን በምድር የተሰጠንን የኑሮ ጊዜ እንገፋለን፡፡ ጊዜ በመስፈርታት ተሸንሽኖ ከ ሳድሲት ሃምሲት፣ ከራብዒት ሳልሲት፣ከካልዒት ኬክሮስ ከኬክሮስ ደግሞ ዕለታት እየተወለዱና ዕለታት አውደ ዕለትን፣ አውደ ወርህን፣ አውደ ዓመትን እየተኩ ና አውደ ዓመትም በበኩሉ ዓውደ አበቅቴ፣ዓውደ ፀሀይ፣አውደ ማሕተብ እየሆነ ግዙፉን ዓውደ ቀመርን ለመደረብ ጊዜ እንደ ወንዝ ወደፊት ብቻ ይፈሳል፡፡ ይህ የማያባራ የዘመን ዶፍ በተደጋገመ የመሬትና የጨረቃ ዙረት እራሱን ይደጋግማል፡፡ ምድርና ጨረቃ ኡደታቸውን ሲጨርሱ መልሰው ያንኑ ኡደታቸውን ይጀምሩና ከቅጽበት (ከካልዒት) ኬክሮስ ከኬክሮስ ዕለታት መልሰው እየተወለዱ ግዙፎቹ ዓዕዋዳት ዳግም ይወለዳሉ፤በዚህ ዙረት ውስጥ አዲስ ቁጥር እንጂ አዲስ ዕለት ወይም ዓመት የለም፡፡ በዘመን ጉዞ ላይ የሰው ልጅ አስተዋጾ ምንም ነው፡፡ በዚህ የጊዜ ፍሰት ውስጥ አዲሱ የሰው ልጅ አካልና መንፈስ ብቻ ነው፡፡ የአካል መታደስን በተመለከተ በየቀኑ 10-50 ትሪሊየን የሚደርሱ የሰውነታችን ሴሎች ሞተው በአዲስ እየተተኩ አዲስ አካላዊ ማንነት ያላብሱናል፡፡ ይህም ደግሞ የተፈጥሮ ህግ ስለሆነ በሰው ይታገዝ ይሆናል እንጂ አይገዛም፡፡ እናም ለሰው እውነተኛው አዲስ ነገር የመንፈስ አዲስነቱ ነው፡፡ የህይወቱ መነሻ የሆነውን የውስጥ ሀሳቡንና በመመርመር መረዳቱን ማስተካከል ወይም መቀየር፣ በመረዳቱ አመለካከቱን የመለወጥና...